በስም ስህተት ነው
ክፍል አንድ
አባ ዘመደ ብርሃን
ሰዓቱ መሽቷል ፡፡ የቦታው አቀማመጥ ቁልቁለት ስለሆነ ወደታች ይገፋተራል፤ አዘቅዝቀው ሲመለከቱት ጨለማው አምሳለ ሲኦል ነው፡፡ ነፋሱ ደግሞ አርጩሜ ይዞ ይጋረፋል፤ የተከናነብነውን ነጠላ ጋቢ ሊናጠቅ ይውተረተራል፡፡ ጭል ጭል በምትለው ባትሪ ብርሃን ጨለማውን እየተጋፋን አባ ዘመደ ብርሃን ተከትለን ጉዞችንን የቁልቁሊት ቀጠልን፡፡
ከአባ ዘመደ ብርሃን ጋር የምንተዋወቀው ከዓመታት በፊት ነው፡፡ ጠይም ረጅም ቁመት፣ ቀጭን ሰውነት፣ በነጭ ሪዝ የተሞላ ፊት፣ አርቆ ማሰብ የሚችል ብሩህ አእምሮ የተሰጣቸው ፤ የሚያስቡትን እግዚአብሔር የሚያሳካላቸው፤ ለመንፈሳዊ ዓላማ የመነኮሱ አባት ናቸው፡፡ ወደ እኛ እየተመለከቱ “አይዞችሁ ልንደርስ ጥቂት ይቀረናል በርቱ ” አሉ፡፡
ቁልቁለቱን እንደጨረስን ወደ ሜዳው ዘልቀን ጉቡታው ላይ ስንደርስ ነጋ፡፡ የቀዘቀዘው ሰውነታችን በጠዋቷ ፀሐይ ተፍታታ፡፡ አቀበቱን መውጣት ስንጀምር አባ ዘመደ ብርሃን “ልጆቼ እዚያ ማዶም ሜዳው ላይ ያለው ጢሻው ጋር ስንደርስ የእመት አይጠግቤ ኃይለኛ ውሻ ስላለ እንዳያስደነግጣችሁ” አሉን፡፡ ቀጠል አድርገው “ውሻው እንደ አሳዳጊው ኃይለኛ እና ክፉ ነው፡፡ አሳዳጊው እመት አይጠግቤ ክፉ ሴት ነበረች ፡፡ ታዲያ ሆን ብላ ሻንቆን ፈትታ የለቀቀችው እንደሆነ፤ በላዩ ላይ ያደረው ርኩስ መንፈስ ጉልበቱ እና ፍጥነቱን ጨምሮለት ያገኘውን ሰውም ይሁን ከብት በጥርሶቹ ቦጫጭቆ ይነክሳል፡፡ ” ብለው በረጅሙ ተነፈሱ፡፡
የእመት አይጠግቤ ታሪክ ስነግራችሁ በእግዚአብሔር ሥራ ትደነቃላችሁ፡፡ የእርሻ ቦታቸውን ፣የጎተራውን እህል፣የደበቁትን ገንዘብ፤ ከፊሉን ለድሆች የተቀረውን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ገዳም በስጦታ ሰጥተዋል፡፡ ኃይለኛውን ሻንቆ እንኳን ንብረት ጠባቂ እንዲሆን ትተውት ሄደዋል፡፡ ለማንኝውም ነገ ቦታው ድረስ ሄደን እንጎበኘዋለን፡፡ በቦታው ላይ ልሠራው ያቀድኩትን የልማት ሥራ ገዳማችን በገንዘብ አቅም ለመደገፍ ያቀድኩትን ሁሉ አስረዳችኋለሁ” ብለው ንግግራቸውን ቋጩት፡፡
አባ ታሪኩን እንዲነግሩን ብንጓጓም፤ ቦታውን ስንጎበኝ ይደርሳል ብለንን በመጽናናት ጉዞአችንን ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያ አቀናን፡፡
ዕድሜ ጠገቡ በሆኑ የዝግባ ዛፎች የተከበበችው የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን፤ ሥሪቷ ክብ ሆና ዙሪያዋን በአረንጎዴ፣ ቢጫ ፣ቀይ ቀለም አጊጦል ፡፡ በጉልላቱ ላይ ያለው መሶበ ወርቅ ከነ መስቀሉ የቤተ ክርስቲያኑ ሞገስ ሆኖ ከሩቅ ይታያል፡፡ በመሶበ ወርቁ ዙሪያው ያለው ወርቃማው ዘርፍ ድምፅ አጥንትን የሚያለመልም የመላእክትን ምስጋና ይመስላል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑን ተሳልመን ስንጨርስ ከቤተ ክርስቲያኑ እልፍ ብሎ በሚገኘው ሰንበቴ ቤት ገብተን፤ በተዘጋጀልን ጠባብ ክፍል ውስጥ በተነጠፈልን ጅባ ላይ ተኛን፡፡ ጎናችን ከምንጣፉ ጋር እንደተገናኘ ሁላችንም እንቅልፍ ጣለን፡፡
“ተነሱ ልጆቼ ሰዓት ደርሷል” የሚል ድምፅ ስሰማ፡፡ ውይ ከመቼው ነጋ
? ብዬ እንቅልፍ ያልጠገበውን ዐይኔን እያሻሸሁ ተነሳሁ፡፡ ቡራኬ ተቀብለን ወደ ቤተ ክርስቲያኑ አቀናን፤ ከጸሎተ ኪዳን በኋላ ጉዞችን ወደ እመት አይጠግቤ ቤት አደረግን፡፡
በአጋም፣ በቀጋ ፣በሰንሰል ችምችም ተደርጎ የታጠረ ሰፊ ግቢ ከመንደሩ ንጥል ብሎ ብቻውን ተቀምጦ ይታያል፡፡ ግዙፉ ዋርካ እና የኮሶ ዛፍ ለጊቢው ሞገስ ሆነውት በኩራት ዝም እንዲል አድርገውታል፡፡ በጥግ በኩል ሰው ገብቶበት የማያውቅበት የምትመስል አጭር ቆርቆሮ በር አለች፡፡ አባ ከፊት ቀድመው በሩ የታሰረበትን ገመድ ፈትተው ወደ ግቢው ዘለቁ፡፡ ገና ወደ ግቢው ስንጠጋ ጀምሮ ሁሉ ነገሩ ጥቁር የሆነ ውሻ መጮህ ጀመረ ፤ ፈርተን ወደ ኋላ ስንል፡፡ አባ ዘወር ብለው “ኑ አይዞችሁ አትፍሩት አይነካችሁም” አሉን፡፡ ኪዚያም “ሻንቆ ብለው ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ተጣሩ” ውሻ በፊታቸው መጥቶ የጫማቸውን ትቢያ መላስ ጀመረ፡፡ አባም “ምነው ሻንቆ እንግዳም አታውቅም እንዴ የምትጮኸባቸው? በል እዚያ ጥግ ድንጋዩ ላይ ተቀመጥ፡፡ እንዳትንቀሳቀስ ዋ! ” አሉት፡፡ ድምፁን አጥፍቶ ጭራውን ሸጉጦ ተቀመጠ፡፡
ወደ ትልቁ ቤት በረንዳ ላይ ወጣን፡፡ አባ ዘመደብርሃን በመስቀላቸው እየጠቆሙ “ይህ ሁሉ ግቢ ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በሥጦታ የተሠጠ ነው፡፡ የእርሻውን መሬት ማሳረስ ጀምሬአለሁ ፤ ከጅረቱ ጠልፌ ወፍጮ ቤት ለማቋቋም ፣ እዚህ ሜዳዉ ላይ ደግሞ የአብነት ትምህርት ቤት መክፈት የወደፊት እቅዴ ነው፡፡ ከዚህ ቦታ ገቢ ብቻ የገዳማችንን መናንያን የዓመት ቀለብ እና የመምህራን ደመወዝ ለማስቻል ምኞት አለኝ ፡፡ እናንተም በእውቀታችሁ እና በገንዘባችሁ እንደተለመደው ከጎኔ ከሆናችሁ ብዙ መልካም ሥራ እንሠራለን፡፡ “ለሁሉም ነገር የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን” አሉ፡፡ መንፈሳዊ ቁጭት በተሞላበት ስሜት፡፡
ልጆቼ ይህን ቦታ የሰጠን ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ “ብዙ ኃጢአት ባለችበት የእግዚአብሔር ጸጋ ትበዛለች” እንዲል ሊቁ ፤ ኃጢአቷ እጅግ በዝቶ የነበረችው ሴት በእግዚአብሔር ችርነት ድና መላ ሕይወቷን ለ እግዚአብሔር ሰጥታለቸ፡፡ ወደ ውስጥ ዘልቃችሁ መደብ ላይ ተቀመጡና ታሪኩን ልንገራችሁ፡፡” ብለው ትረካቸውን ለመጀመር ተዘጋጁ ፡፡
ከአፍታ ቆይታ በኋላ
ክፍል ሁለት ይቀጥላል
ያዕቆብ ሰንደቁ
ሚያዚያ 1 2008ዓ.ም
አዲስ አበባ
ምንም አስተያየቶች የሉም:
አስተያየት ይለጥፉ