“እኛ የሰማይ ቤታችንን ትሠራልናለህ ስንል፤ አንተ ግን ኃላፊውን ቤት ”
በቅርቡ ናጄሪያ ውስጥ አንድ የሃይማኖት ተቋም ለአምልኮ ሥፍራ ግንባታ እያካሄደ እያለ የተሾመው አገልጋይ ሲሚንቶውን፣ ብረቱን እየወሰደ ገንዘቡን እመዘበረ የራሱን ቤት ይሠራል፡፡ ይህን ያዩ ሰዎች አዝነው ከኃላፊነቱ እንዲነሳ ያደርጉታል፡፡
ይህን መጥፎ ምግባር አምርሮ ይጠላ የነበረ ሌላ አገልጋይ ይሾማል፡፡ የተሾመው አዲስ አገልጋይ የአምልኮ ቦታውን ግንባታ መጎተቱን አይቶ ሥራውን ያፋጥናል፤ ሙስናንም ይጠየፋል ተብሎ ተስፋ ተጣለበት፡፡ አገልጋዩም ሥራውን ከተቀበለ ወራት አለፈ፡፡ የአምልኮ ቦታው ግንባታ ግን ጭራሹኑ ቆመ፡፡
አዲሱ ተሾሚ አገልጋይ ለግንባታ በተመደበው በጀት በውድ ዋጋ መሀል ከተማ መሬት ገዝቶ ባለ አራት ፎቅ ቤት ለራሱ መሥራት ጀመረ፡፡ በፍጥነት ብቅል ያለው ሕንጻ መነጋገሪያ ሆነ፡፡ አገልጋዩም ሲሚንቶውን፣ ብረቱንም ቁሳቁሱንም እየወሰደ የራሱን ቤት መገንባቱን አፋጠነው፡፡
ሁኔታውን ያዩት አማኞች “ገንዘባችን ተዘረፈ የባሰው መጣብን” ብለው ጮሁ፡፡ ከዚያም ስብሰባ እንዲጠራ አደረጉ፡፡ አገልጋዩንም ጠርተው “የአምልኮ ቤታችንን ግንባታ አቁመህ የራስህን ቤት ሠራህ ኃላፊነትህ አስረክቡ” ብለው ጮሁበት፡፡ አገልጋዩም ሰውን ሳያፍር ፈጣሪን ሳይፈራ በኩራት “የመጣው ይመጣል እንጂ በፍጹም አገልግሎቴን አልተውም ” ብሎ ድርቅ አለ፡፡ ሕዝቡም አጥብቆ “ገንዘባችን ዘርፈሀል በፍጥነት ልቀቅ ” ብለ ተቆጡ፡፡
አገልጋዩም የነገሩን መጋጋል አይቶ “እባካችሁ በፈጣሪ ስም እለምናችኋለው የጀመርኩትን ፎቅ ቤት እስክጨርስ ድረስ ታገሱኝ፤ ከዚያ አገልግሎቴን አቆማለው” ብሎ አረፈው፡፡ ሕዝቡም “እኛ የሰማይ ቤታችንን ትሠራልናለህ ስንል፤ አንተ ግን ኃላፊውን ቤት ሠራህ” ብለው ጉዳዩን ወደ ሕግ ወሰዱት፡፡
ምንም አስተያየቶች የሉም:
አስተያየት ይለጥፉ